søndag 2. februar 2014

ሰማያዊ ፓርቲ በብዙ አፈና ታጅቦ በጎንደር የጠራውን ሰላማዊ ሰልፍ አከናወነ


“ተከብሮ በኖረው በአባቶቻችን ደም
እናት ኢትዮጵያ ያስደፈረሽ ይውደም”
ዛሬ በጎንደር ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ሕዝብ በአንድ ላይ የሃገሩን ድንበር ተቆርሶ ለሱዳን መሰጠቱን ለመቃወም የዘፈነው ዘፈን ነው። ገና ከቅስቀሳው ጀምሮ በስርዓቱ ፖሊሶችና የደህነት ሰራተኞች የዛሬው ሰልፍ እንዳይሳካ ከፍተኛ የሆነ መሰናክል ቢገጥመውም በጎንደር የተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ በሰላም ሲጠናቀቅ፤ አንዳንድ የሰማያዊ ፓርቲ ደጋፊዎች እና አባላት አሁንም ከሰልፉ በኋላ መታሰራቸው አልቀረም።
በሰልፉ ቅስቀሳ ወቅት የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ የጎንደር አባላት እና ደጋፊዎች “ሕገ ወጥ ስልፍ ነውና አትቀስቅሱ” በሚል ታስረው የተፈቱ ቢሆንም “ሕገ መንግስታዊ መብታችን መንግስትን ሰላማዊ ሰልፍ እንደምናደርግ ማሳወቅ እንጂ ማስፈቀድ የለብንም” በሚል እስከ መጨረሻው ድረስ ባደረጉት ትንቅንቅ እየታሰሩ መፈታት፣ መንገላታት ቢደርስባቸውም ሰልፉ ዛሬ በጎንደር ከተማ ተደርጓል።
gonder-2-blue
በጎንደር መስቀል አደባባይ በርካታ የከተማው ነዋሪዎች ወጥተው ለሱዳን የተሰጠውን እና የሚሰጠውን መሬት ጉዳይ የተቃወሙ ሲሆን መንግስት የሃገርን ዳር ድንበር ከመሸጥ ተግባር እንዲቆጠብ ጠይቀዋል። መሬት ከመስጠት እንዲቆጠብ ከመጠይቅም በላይ መንግስት በአሁኑ ወቅት በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያ መረጃ እየሰጠ ባለመሆኑ፤ በተቃራኒው የሱዳን መንግስት ስለተበረከተለት መሬት በሚዲያዎቹ በሰፊው እየለፈፈ በመሆኑ፤ ለሕዝቡ መረጃ የመስጠት ግዴታ አለበት ሲሉ የተቃውሞ ሰልኞቹ መጠየቃቸውን ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ አመልክቷል።
ለዘ-ሐበሻ እንደደረሰው መረጃ ከሆነ የጎንደር ከተማ ትራፊክ ፖሊስ ከበላይ በመጣ ቀጭን ትዕዛዝ በዚህ ታሪካዊ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ለመታደም ወደዚያው የሚተመውን የጎንደር ሕዝብ የትራፊክ መንገድ በመዝጋት ወደ መስቀል አደባባይ እንዳይሄድ ሲያከላክል እንደነበር ተገልጿል። 5ለ1 የተደራጁ የሥርዓቱ ደጋፊዎች ወደ ሰልፍ ለመሄድ የሚዘጋጁትን እና እየሄዱ ያሉትን ለማሸማቀቅ ቢሞክሩም ሕዝቡ ወጥቶ ድምጹን ከማሰማት እንዳላገደው መረጃው ያመለክታል። እነዚሁ ኢህአዴግ 5ለ1 ያደራጃቸው ግለሰቦች (ጠርናፊና ተጠርናፊዎች) ሰልፉ ተሰርዟል በሚል በጎንደር ሰፊ ቅስቀሳ ባማድረግ ነጻ ሚድያ የማይሰማውን ሕዝብን ሲያሳስቱ እንደነበር ተገልጿል።
ዛሬ በጎንደር የተደረገውን ሰላማዊ ሰልፍ ያስተባበሩት ለህብረተሰቡ በሰላማዊ ሰልፉ ላይ ባሰሙት ንግግር “በዚህ አስቸጋሪ ወቅትና አምባገንን ስርዓት ውስጥ ሆናችሁ፤ የሀገራችን ጉዳይ ያገባናል ብላችሁ ስለመጣችሁ እናመሰግናለን” ካሉ በኋላ ሰላማዊ ሰልፉ ታዳሚ ይህ ሰልፍ ለምን ሊደረግ እንደቻለ አብራርተዋል። በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያም ገለጻ አድርገዋል።
በሰልፉ ላይ የተገኙት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በበኩላቸው “ወጣቶች የሃገራችሁን ክብር ለማስጠበቅ ራሳችሁን ከፍርሃት አላቁ። ከፍርሃት እና ከሥጋት ወጥታችሁ ለሃገራችሁ አለኝታ ሁኑ” ብለዋል። ለሥርዓቱ መሪዎችም “ሥልጣን ወቅታዊ ነው፤ ያልፋል። በኢትዮጵያ ዳር ድንበር ላይ የሚጸመው ደባ ግን አያልፍም” ካሉ በኋላ ይህን ታሪካዊ ስህተት እንዲያስቆሙ በንግግራቸው ላይ እንደጠየቁ የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ከጎንደር ዘግበዋል።
“የኢሕአዴግ ባለስልጣናት ለልጆቻቸው ጥሩ ታሪክን እንጂ ውርደትን ማውረስ የለባቸውም” በማለት የተናገሩት ኢንጂነር ይልቃል በኢትዮ-ሱዳን ድንበር ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ዛሬ ፌብሩዋሪ 2 ቀን 2014 በጎንደር በተደረገው ሰላማዊ ሰልፍ ሕዝቡ
“ሉዓላዊነታችንን አናስደፍርም”
“ወያኔ አይወክለንም”
“እናት ኢትዮጵያ የደፈረሽ ይውደም”
“አባቶቻችን ያስረከቡንን መሬት አሳልፈን አንሰጥም” የሚሉም የተቃውሞ መፈክሮችን ሲያሰማ ነበር።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar