lørdag 10. august 2013

ድምጻችን-ይሰማ፦ የመጀመሪያው በሳል ኢትዮጵያዊ ሰላማዊ ትግል

ድምጻችን-ይሰማ፦ የመጀመሪያው በሳል ኢትዮጵያዊ ሰላማዊ ትግል 

ከያሬድ አይቼህ

ህወሃት ደደብ ነው። ምንም የማይገባው ፡ ገደብ የማያቅ ፡ ግርድፍ ባዕዳዊ ድርጅት ነው። በአስተሳሰቡ ባዕድ ፡ በስነምግባሩ ባዕድ ፡ በግብረገቡ ባዕድ። ይሄን የህገ-አራዊት ድርጅት ፊት ለፊት የገጠመው የድምጻችን-ይሰማ ንቅናቄ ነው። የንቅናቄው ብስለት ፡ አርቆ አሳቢነት ፡ አገራዊነት እና ሰብዓዊነት ድንቅ ነው ፤ ድንቅ!
ከ18 ወራት በፊት አካባቢ የጀመረው የድምጻችን-ይሰማ ንቅናቄን በመጠኑ ግራ በመጋባት እና በተደባለቀ ስሜት ስከታተል ቆይቻለሁ። በዩናይትድ ስቴትስ የምንኖር ሰዎች የአሜሪካንን ፊሪሃ-ኢስላም (islamophobia) ፕሮፓጋንዳ ሌት ተቀን ስለምንጋተው ፡ እኔም ፈሪሃ-ኢስላም ተጠናውቶኝ ነበር። “ለመሆኑ የኢትዮጵያ ሙስሊሞችም አሸባሪነትን ያስተናግዱ ይሆን?” የሚለው ጥያቄ በአይምሮዬ ጀርባ ሲያንዣብብ ቆይቷል።
ልጅ ኢያሱ መሃመድ አሊ (100 ዓመት)
የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ታሪካዊ የሆነ የመንግስታዊ ተቋም ጫና እና ጭቆና እንደ ደረሰባቸው አምናለሁ። ልጅ ኢያሱ መሃመድ አሊን እንዳይነግስ ያገደው መንግስታዊ ፈሪሃ-ኢስላም ፡ በሌሎች ታሪካዊ ክስተቶችም ጫናውን እና ጭቆናውን ማሳየቱ የሚካድ አይደለም።
ሆኖም ግን አራዊቱ ህወሃት በ21ኛው ክፍለ ዘመን ፈሪሃ-ኢስላምን ተጠቅሞ መጅሊሱን (የኢትዮጵያ ሙስሊም ማህበርን) ለመቆጣጠር መፈለጉ ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች አሁንም የመንግስት ተቋማዊ ጭቆና ቀንበር ፡ ከልጅ ኢያሱ መሃመድ አሊ ከስልጣን መባረር 100 ዓመት በኋላ ፡ ደግሞ መከሰቱ ሙስሊሞች መብታቸውን ካለስከበሩ ማንም እንደማያስከብርላቸው የሚያስረግጥ ሃቅ ነው።
የ18 ወራት ፈተና
ድምጻችን-ይሰማ ላለፉት 18 ወራት እንደ ወርቅ ተፈትኗል። መሪዎቹ ታስረዋል። ያልተለወጠው ነገር ቢኖር ግን የንቅናቄው ብስለት ፡ አርቆ አሳቢነት ፡ አገራዊነት እና ሰብዓዊነት ናቸው። ንቅናቄው በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ ለመብታቸው ለሚታገሉ ዜጎች ፡ ቡድኖች ፡ ድርጅቶች ሁሉ ትልቅ አርአያ ነው።
የድምጻችን-ይሰማን አርአያነት በመከተል ሌሎች ንቅናቄዎች ህገመንግስታዊ መብቶች እንዲከበሩ ፋና ወጊ ሰላማዊ ትግልን ማራመዳቸው አይቀሬ ነው። የንቅናቄው ራሱን መግዛት ፡ ለአራዊቱ ህወሃት ወጥመዶች ራሱን አሳልፎ አለመስጠት ፡ በጽናት ጥያቄዎቹን በአርብ ጸሎት ላይ ማሰማቱ እጅግ ድንቅ ነው። ፍርሃት የማይበግረው ፡ የአውሬው ወያኔ ሚዲያ የማያግደው ፡ የሰላማዊ ትግል ጀግኖች ንቅናቄ በኢትዮጵያ ባለፉት 18 ወራት ተወልዷል።
የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስላለች
አንዳንድ መሰሪ ፡ መርዛም ግለሰቦች የድምጻችን-ይሰማን ንቅናቄ “ለምን ለሁሉም ጥያቄ አይታገሉም?” የሚል የጥገኛነት ትችት ሊያሰራጩ ሲሞክሩ ፡ በተለይ ‘ሲቪሊቲ’ በሚባለው የፓልቷክ የዉሃ ላይ ኩበቶች ስብሳቤ ክፍል አዳምጫለሁ። ለራሴ ነፃነት ሃለፊነቱ የእኔ ነው።

በዲያስፓራ ተቀምጠን ፊትለፊት ያለምንም ፍርሃት አራዊቱን ወያኔ የሚጋፈጡትን የሰላማዊ ታጋዮች መተቸት የሞራል ዝቅጠት ፡ የስነልቦናን ውርደት እና የሰብአዊነት ኪሰራን የሚያሳይ ነው። የዲያስፓራ ቱልቱላዎች እረፉ። ባታርፉም ምንም ስለማታመጡ እረፉ።
ድምጻችን-ይሰማን መቃወም አራዊቱን ወያኔን መደገፍ ነው። ፈሪሃ-ኢስላም ያላችሁ ሰዎች ፡ የድምጻችን-ይሰማን የትግል መስመር ፡ ፈተና እና ጽናት ብታጤኑ እንደ እኔ ከፍርሃታችሁ ነጻ ትወጣላችሁ።
ድምጻችን-ይሰማ ግፋ! ቀጥል! በአላማህ ጽና!
ክብር ለሰማዕታት!
ኢድ ሙባረክ።
- – -

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar