torsdag 12. juni 2014

ቴዲ አፍሮ ኮካ ኮላ ባለፈው ሳምንት ላወጣው መግለጫ የሰጠው ምላሽ

ቴዲ አፍሮ ኮካ ኮላ ባለፈው ሳምንት ላወጣው መግለጫ የሰጠው ምላሽ

  • 1589
     
    Share
አስከመጨረሻው የዓለም ዋንጫ መከፈቻ ዕለት የመጨረሻ ሴኮንድ ድረስ እንጠብቃለን፡፡
989TeddyAfro_NYC_26

አስከመጨረሻው የዓለም ዋንጫ መከፈቻ ዕለት የመጨረሻ ሴኮንድ ድረስ እንጠብቃለን፡፡
ሰኔ ግንቦት 23 2006 አለአግባብ እንዳይለቀቅ በተደረገው የዓለም ዋንጫ የኢትዮጵያው ቅጂ ሙዚቃ አስመልክቶ ያለንን አቋም በመግልፅ መግለጫ ማውጣታችን ይታወሳል፡፡
ምንም እንኳን መግለጫውን በድረ ገፃችን ላይ አትመን ለማውጣት ከመወሰናችን በፊት ጉዳዩን በተመለከተ ለኮካ ኮላ እና ወኪሉ ለሆነው ማንዳላ ቲቪ አስቀድመው እንዲያውቁት ብናደርግም እስከ አሁን ድረስ ምንም ዓይነት ምላሽ አላገኘንም፡፡ የዚህ ዓይነቱ ባህሪ ላለፉት በርካታ ወራቶች ተደጋግሞ ሳያቋርጥ የገጠመን በመሆኑ የሚያስደንቀን አልሆነም፡፡
እኛን ባስደነቀን መልኩ “ታዲያስ መጋዚን” በተሰኘ ድረ ገፅ ላይ ባለፈው ግንቦት 30 ቀን 2006 ዓ.ም ኮካ ኮላ ያወጣውን መግለጫ ለመመልከት የቻልን ሲሆን ምንም እንኳን ይህው መግለጫ በቀጥታ ለእኛ ያልደረሰን ቢሆንም ለክቡራን አድናቂዎቻችን በመግለጫው ውስጥ የተካተቱት ጭብጦች ምንም ዓይነት የውል፣ የፍሬ ነገር እና የህግ መሰረት የሌላቸው መሆኑን ማብራራቱ እና መግለፁ አግባብነት ይኖረዋል ብለን አምነናል፡፡
መግለጫው ቴዲ አፍሮ ከኮካ ኮላ ጋር እንዴት እና ለምን ግብ ግንኙነት እንዳደረገ እንደሚከተለው በማተት ይጀምራል፤ “ቴዲ አፍሮ አፍሪካ ባለው የኮካ ሰቱዲዬአችን የመጣው የኮካ ኮላ ቅጂ የሆነውን “ዓለም የኛ ነች” የተሰኘውን የፊፋ የዓለም ዋንጫ ሙዚቃ ልዩ ዓይነት የሆነውን ኢትዮጵያዊ ሙዚቃ ለማሰቀረፅ በታቀደ ግብ ነበር” ይላል መግለጫው፡፡
ይሁን እንጂ መግለጫው ማን “እንዳመጣው” እና ምርጫውንም እንዳደረገ አያመለክትም ወይም አይገልፅም፡፡ በመግለጫችን ላይ እንዳብራራነው ለኮካ ፕሮጄክት ወደ እኛ በመቅረብ ምርጫውን በማድረግ ተነሳሽነቱን የወሰደው አቶ ምስክር ሙሉጌታ ከመሆኑ በተጨማሪ ይህው ስው ከኮክ ሰቱዲዮ ጋር በማገናኘት ከኮካኮላ ማዕከላዊ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ አፍሪካ ሊሚትድ ወኪል ከሆነው ከማንዳላ ቲቪ ጋር ውል እንድንዋዋል አድርጓል፡፡
ከአቶ ምስክር እና ከማንዳላ ቲቪ ጋር ኮካ ኮላ በቅደም ተከተል የአሰሪ እና ሰራተኛ እንዲሁም የወኪል እና የወካይ ግንኙነት ያለው ቢሆንም በመግለጫው ላይ አንዳችም ዓይነት ግንኙነት ስለመኖሩ ከማስተባበሉ አልፎ በመሄድ “ከቴዲ አፍሮ ጋር የተደረገው ውል ማንዳላ ሊሚትድ በተሰኘ እና መቀመጫው ናይሮቢ በሆነ አዘጋጅ ተቋም “በ3ኛ ወገን” በኩል የተፈፀመ ነው” በማለት በአፅንኦት ገልጾ ራሱን ከነበረው ትስስር ነጥሏል፡፡
3ኛ ወገን የሚለው ቃል …..የስምምነት ወይም የግብይት…. ወገን ያልሆነ እና አልፎ አልፎ ከስምምነቱ ወይም ከግብይቱ ውጪ የሆነ ወገን ተብሎ ይገለፃል፡፡ እንደ ኮካ ኮላ መግለጫ ከሆነ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ የኮካ ኮላ ብራንድ ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ ምስክር ሙሉጌታ እና ለኮካ ኮላ በኮካ ስቱዲዮው በኩል ሙዚቃ ነክ ንብረቶችን ለማዘጋጀትና ለማስተዋወቅ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚያቀርብለት ወኪሉ ማንዳላ ቲቪ ኮካ ኮላ ከአደረገው ስምምነት እና ግብይት እንዲሁም በመግለጫው ላይ “የኮካ ሰቱዲዬአችን” በሚል ፍንትው ባለ አገላለፁ ካመለከተው ጋር አንዳችም ግንኙነት የሌላቸው ባይታወሮች ናቸው፡፡
አቶ ምስክር እንደ ተቀጣሪ ሰራተኝነታቸው እና ማንደላ ቲቪም እንደ ወኪልነቱ ልዩ ልዩ ሙዚቃ ነክ ንብረት አገልግሎቶች ለማከናወን በመዋዋል በማዕከላዊ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ አፍሪካ ኮካ ኮላ ምትክ እና ፋንታ ህጋዊ ተግባራታቸውን ሲፈፅሙ ልክ ዋና መስሪያ ቤቱ አትላንታ ለሚገኘው እና መግለጫውን እንዳወጣው የኮካ ኮላ ተወካይ አንድ ዓይነት የሆነ የህግ ችሎታ/አቋም እና ውጤት አላቸው፡፡
ይህ በራሱ ተቀጣሪ ሰራተኛ እና በወኪሉ መካከል ያለውን የፍሬ ነገር እና የህግ ትስስር ሙሉ ለሙሉ በመካድ ኮካ ኮላ ባወጣው መግለጫው ላይ “ሶስተኛ ወገን” የሚል ከቶም አግባብነት በሌለው ቃል ተክቶ ራሱን ከማናቸውም ግንኙነት ለማራቅ ምክሯል፡፡ ይህም ሁኔታ በቅዱስ መፅሐፍ ላይ ጲላጦስ የፈፀመውን ፈፅሞ “ከደሙ ንፁህ ነኝ” ያለውን ጥቅስ ያስታውሰናል፡፡
ይህ ክብርን የሚያቃልል እና የሚነሳ መግለጫ የሰው ልጅን፣ የሁሉም አድናቂዎቻችንን እና የኮካ ኮላንም ደንበኞች ጭምር ዕውቀት፣ አእምሮ እና ግንዛቤ የሚገዳደር እና የሚፈታተን ነው፡፡ ይህም አድራጎቱ ቆሜለታለሁ ከሚለው የኩባኒያው የስነ ምግባር መርሆዎች ማለትም ከመልካም ስብእና፣ ታማኝነት፣ የህዝብ አመኔታ እና አሌኝታነት ጋር የሚፃረርም ነው፡፡
በእርግጥ ኮካ ኮላ ከቴዲ አፍሮ ጋር ማናቸውም ዓይነት ግንኙነት ከሌለው እንግዲያውስ በአጠቃላይ መግለጫውን ለማውጣትና ከሁሉም በላይ ደግሞ ቴዲ “ለአደረገው ጥረቱ ሙሉውን” የተከፈለው ስለመሆኑ እና “የተሰራው ሙዚቃ የማዕከላዊ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ አፍሪካ ኮካኮላ ንብረት ሆኗል” በማለት አፅንኦት ሰጥቶ ለማረጋገጥ ለምን አሰፈለገው?”
አሳዛኙ ነገር ላለፉት ወራቶች ከኮካ ኮላ እና ከማንዳላ ቲቪ ጋር ስናደርግ በነበረው የቃል እና የፁሁፍ ግንኙነቶች ተመሳሳይና አስደንጋጭ ጎጂ ተግባራቶችን ስንቀበልና ስናስተናገድ ቆይተናል፡፡ እነኚህ ድርጊቶች ከቅን ልቦና የመነጩ ወይም የዕውቀት ማነሰ ውጤት ናቸው የሚል ዕምነት የለንም፡፡ ይልቁንም ሆን ተብሎ የሚፈፀም ፍፁም ተቋማዊ የማናለብኘነት አድራጎት ነው፡፡
ይህም ቢሆን ግን ራሱን በሚያከበር ኢትዮጵያዊ በሚመጥን ትዕግስት፣ ትህትና እና አክበሮት በጉጉት መለቀቁ እየተጠበቀ ያለውን ሙዚቃ ወይም ሊለቀቅ የማይችልበትን ምክኒያት አስከመጨረሻው የዓለም ዋንጫ መከፈቻ ዕለት የመጨረሻ ሴኮንድ ድረስ እንጠብቃለን፡፡

በዞን 1 የሚገኙት ጀግኖቻችን በዛሬው እለት ተበታትነው እንዲደለደሉ ተደረገ! በህዝበ ሙስሊሙ ወኪሎች ላይ በማረሚያ ቤት እየተደረገ ያለው ወከባ በአስቸኳይ ይቁም ! (ድምፃችን ይስማ)


በሐሰት የሽብር ክስ ህገ መንግስታዊ መብቶችን በጣሰ ሁኔታ መሪዎቻችንን እያጉላላ የሚገኘው መንግስት በማረሚያ ቤት ውስጥ የሚያደርገውን ወከባ ቀጥሎበታል፡፡ ገና ወደማረሚያ ቤት ከተዛወሩበት ጊዜ አንስቶ ጠያቂዎችን በማጉላላት፣ የጥየቃ ሰአትን ከሌሎች በተለየ መልኩ በመገደብ፣ እንዲሁም በጠያቂዎች ቁጥር ላይ ገደብ በማድረግ በተለያዩ ወቅቶች መብታቸውን ሲነግፍ የቆየው መንግስት ዛሬ ደግሞ በታሪካዊው የካንጋሮ ፍርድ ቤት የችሎት ሂደት ምስክሮቻቸውን እያቀረቡና ትክክለኛው የህዝበ ሙስሊሙ ትግል ገጽታ በችሎት እየተመሰከረ ባለበት በዚህ ወቅት በፍርድ ቤት እየደረሰበት ያለውን ሽንፈት ለመቋቋም ወኪሎቻችን ላይ የተለያዩ ወከባዎችን እየፈጸመ ይገኛል፡፡ እስካሁን ድረስ በእስር ቤቱ ታሪክ በምንም መልኩ የማያስጠይቅን፣ ይልቁንም በማረሚያ ቤቱ ደንብ ጥበቃ የተደነገገለትን ገንዘብ የመያዝ መብት እንደወንጀል በመቁጠር በኮሚቴው ሰብሳቢ ኡስታዝ አቡበከር አህመድ እና በሸኽ መከተ ሙሄ ላይ፣ እንዲሁም በሌሎች ታሳሪዎች ላይ ሲያደርስ የነበረውና በቅርቡ የተረጋጋው ወከባ መሪዎቻችንን የማጥቂያ ሰበብ ፍለጋ እንጂ ሌላ እንዳልሆነ ግልጽ ነበር፡፡Ethiopian Musilms
አሁንም ይህንኑ ህገወጥ ድርጊቱን የቀጠለበት የእስር ቤቱ አስተዳደር በዞን አንድ በሚገኙ ጀግኖቻችን፣ (ማለትም በሸኽ መከተ ሙሄ፣ በኡስታዝ አቡበከር፣ በኡስታዝ ካሚል ሸምሱ፣ በኡስታዝ አህመድ ሙስጠፋ፣ በጋዜጠኛ አቡበከር ዓለሙ፣ በወንድም አብዱረዛቅ አክመል እና በወጣት ሙባረክ አደም) ላይ በዞን አንድ በሚገኙት 8 ክፍሎች እንዲበታተኑና እንዲለያዩ ትእዛዝ አስተላልፏል፡፡ ጓዞቻቸውንም ወደየተመደቡበት ክፍሎች እንዲቀይሩ እንደተነገራቸው ታውቋል፡፡ ባለበት የጤና ችግር ምክንያት ልዩ ትኩረትና ረዳት ጓደኛ የሚያስፈልገውን ወንድም አብዱረዛቅን ድጋፍ ለማግኘት አስቸጋሪ እንደሚሆንበት እያወቁ ብቻውን መድበውታል፡፡ ኡስታዝ አህመድ ሙስጠፋንም እንዲሁ ጊዜያዊ ማቆያ ተብሎ በሚታወቀውና በእስረኞች ቶሎ ቶሎ ተለዋዋጭነት ምክንያት ማህበራዊ ትስስር መመስረት አስቸጋሪ በሆነበት ክፍል ሆን ተብሎ እንዲመደብ ተደርጓል፡፡
የማረሚያ ቤቱ ደንብ በአንድ የክስ መዝገብ ችሎት የሚከታተሉ ታራሚዎች በችሎታቸው ዙሪያ በየጊዜው መነጋገርና መወያየት እንዲችሉ በአንድ ዞን የመታሰር መብት የሚሰጥ ቢሆንም አስተዳደሩ ግን ይህንን የሚያደርገው ሆን ብሎ የችሎታቸውን ፍሰት ለማስጓጎል እንደሆነ የአደባባይ ምስጢር ሆኗል፡፡ ሆነ ተብሎ እነሱን ብቻ የለየ ጥቃትና የመብት ጥሰት የሚፈጸምባቸውም በእስር ቤት ውስጥ ባለቻቸው ውስን ነጻነት የገነቧትን ማህበራዊ ትስስር ለማፍረስና የመጪውን ረመዳን ጾምም ተረጋግተው መጾም እንዳይችሉ ጫና ለማሳደር መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ አወዛጋቢው የፍርድ ሂደት ቀጥሎ የሰው ምስክርነት እየተደመጠ ባለበት ሁኔታ የመጨረሻ ውሳኔ የማስለወጥ ሃይል ባይኖረውም እየተደመጠ ያለው ምስክርነት እጅግ እንዳደናገጣቸውና በዚህም ይህንን እርምጃ ለመውሰድ እንደተገደዱም የሚያሳብቅ ሆኗል፡፡ መንግስት በሃሰት የሽብር ክስ ማንገላታቱ ሳያንሰው በእስር ቤት ውስጥ እንኳን ታራሚዎች ላይ የሚያደርሰው በደል በእርግጥም የአገሪቱ የፍትህ ስርአት የቁልቁለት ጉዞውን እያፋጠነ ለመሆኑ ከበቂ በላይ ምስክር ነው፡፡
የእስር ቤቱ አስተዳደር ውስጥ ያሉት አንዳንድ ሀላፊዎች በግፍ እስር ላይ ለሚገኙት የህዝበ ሙስሊሙ ወኪሎች ያላቸውን ጥላቻ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲያሳዩ መቆየታቸው ይታወቃል፡፡ ካሁን ቀደም የደሴ ወጣት ታሳሪዎች ወደጨለማ ክፍል እንዲገቡ መወሰኑን ተከትሎ ሌሎች እስረኞች ተቃውሟቸውን ለማሰማት በተሰበሰቡበት ወቅት በቅጽል ስሙ ሻእቢያ ተብሎ የሚጠራው የማረሚያ ቤቱ የጸጥታ ሀላፊ ‹‹እኒህን አሸባሪዎች ይህን አጋጣሚ ተጠቅሞ መረሸን ነበር!›› ብሎ ቁጭቱን ሲገልጽ በግላጭ የተሰማ ሲሆን በተለያዩ አጋጣሚዎችም ጥቃት ከመፈጸም ወደኋላ እንደማይሉ መታዘብ ተችሏል፡፡ በማረሚያ ቤቱ ግቢ ውስጥ ካሁን ቀደምም በሌሎች በርካታ ታሳሪዎች ላይ አሰቃቂ የጅምላ ድብደባ ሲፈጸም የነበረ መሆኑ የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው፡፡
ህዝበ ሙስሊሙ ይህን መሰል የህገ መንግስቱን የእስረኛ አያያዝ ደንብ በግላጭ የሚጥሱ ወከባዎችና በደሎች በአስቸኳይ እንዲቆሙ ይጠይቃል! ህዝበ ሙስሊሙ ላይ ያወጁትን ጦርነት ሲያስፈጽሙ የቆዩት ደህንነቶችና የመዋቅራቸው አካላት ከህግ በላይ የሆነ አካሄዳቸውን በአስቸኳይ እንዲያቆሙም ያሳስባል! በህዝበ ሙስሊሙ ወኪሎች ላይ የሚፈጸም ማንኛውም ወንጀል በህዝበ ሙስሊሙ ላይ የሚፈጸም ወንጀል ነው፡፡ እነርሱ ላይ የሚደርስ በደል ፈርሞ ወደመንግስት በላካቸው ሰፊው ህዝበ ሙስሊም ላይ የሚደርስ በደል ነው፡፡ በመሆኑም በወኪሎቻችን ላይ አንዳች ነገር ቢደርስ ሃላፊነቱን ሙሉ በሙሉ የሚወስደው መንግስት መሆኑን እያስታወቅን ሰላማዊው ህዝበ ሙስሊምም ይህን መሰሉን ድንበር ያለፈ ጥቃት እስከመጨረሻው የሚፋረደው መሆኑን በጥብቅ እናሳውቃለን!
በህዝበ ሙስሊሙ ወኪሎች ላይ በማረሚያ ቤት ውስጥ እየተደረገ ያለው ወከባ በአስቸኳይ ይቁም!
የእስር ቤቱ አስተዳደር ከህግ በላይ መሆኑን በአስቸኳይ ያቁም!
የህዝብ ወኪሎችን ማጉላላት ይብቃ!
ድምፃችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!